በተለያዩ ክልሎች በመገንባት ላይ ያሉ የሃይል ማመንጫ ፕሮጄክቶች በበጀት እጥረት ሳቢያ ግንባታቸው መስተጓጎሉ ተገለጸ

ኢሳት (ጥር 8፥ 2009)

መንግስት ያጋጠመውን የፋይናንስ እጥረት ተከትሎ በተለያዩ ክልሎች በመገንባት ላይ ያሉ የሃይል ማመንጫ ፕሮጄክቶች በበጀት እጥረት ሳቢያ ግንባታቸው መስተጓጎሉ ተገለጸ።

በሀገሪቱ በመካሄድ ላይ ስላሉ የሃይል ማመንጫ ፕሮጄክቶች ሪፖርትን ያደመጠው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባለፉት ስድስት ወራቶች ፕሮጄክቶቹን ለማጠናቀቅ ሲካሄዱ የነበሩ እንቅስቃሴዎች አፈጻጸም ዝቅተኛ መሆኑን አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ዋና ስራ አስፈጻሚ የሆኑት ኢንጂነር አዜብ አስናቀ ፕሮጄክቶቹ በተቀመጠላቸው ጊዜ ግንባታቸው እንዳይከናወን የበጀት እጥረት ማጋጠሙን ለፓርላማ አስረድተዋል።

ለተቋራጮቹ ሊከፈል የሚገባው ቅድመ-ክፍያ በወቅቱ አለመከፈልና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ለአፈጻጸሙ ዝቅተኛነት ዋነኛ ምክንያት መሆናቸው ሃላፊዋ ለፓርላማ መግለጻቸውን የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

ይሁንና የትኞቹ የሃይል መመንጫ ፕሮጄክቶች በበጀት እጥረት ምክንያት መስተጓጎል እንዳጋጠማቸው የተገለጸ ነገር የለም።

መንግስት ያጋጠመውን ይህንኑ የፋይናንስ እጥረት ለመቅረፍ ተቋራጮች በራሳቸው ገንዘብ የፕሮጄክቶቹን ግንባታ እንዲያከናውኑ እና ገንዘቡ በሂደት እንደሚተካላቸው በማግባባት ስራዎች እንዲከናወኑ ጥረት መደረጉንም ሃላፊዋ አክለው አስታውቀዋል።

ፕሮጄክቶቹ በመገንባት ላይ ያሉት ተቋራጮች ሃሳቡን ይቀበሉት አይቀበሉት ግን የታወቀ ነገር የሌለ ሲሆን፣ ባልፈው አመት ወደስራት ይገባሉ ተብለው የነበሩ ፕሮጄክቶች በጅምር ላይ መሆናቸውም ታውቋል።

ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም ደሳለኝ ሃገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት እንዳጋጠማት ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል። ይኸው የውጭ ምንዛሪ እጥረት በኢትዮጵያ የፋይናንስ ኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች ይገልጻሉ።

የአባይ ግድብ ግንባታን ጨምሮ ሌሎች የሃይል ማመንጫ ፕሮጄክቶችን ለማከናወን መንግስት ከቻይና መንግስትና ከሌሎች አበዳሪ አካላት ብድር ሲወስድ መቆየቱ ይታወቃል።

ይሁንና መንግስት እየወሰደ ያለው ብድር ከመጠን በላይ እየጨመረ በመምጣቱ መንግስት እያካሄደ ላላቸው ፕሮጄክቶች ሌላ አማራጭን ለመከተል እንደተገደደ የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች በመግለጽ ላይ ናቸው። መንግስት አጋጥሞት ያለውን የፋይናንስ ችግር ለመቅረፍ ትርፋማ የተባሉ መንግስታዊ ድርጅቶችን ሳይቀር በሽርክና ለማስተዳደር መወሰኑ ይታወቃል።

ሰሞኑን ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫን የሰጡት አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ መንግስት የኢትዮጵያ መርከብ አገልግሎት ድርጅትን ከውጭ ኩባንያዎች ጋር በሽርክና ለማስተዳደር መወሰኑን ይፋ አድርገዋል።

የምጣኔ ሃይት ባለሙያዎች በበኩላቸው መንግስት ያጋጠመውን የፋይናንስ ችግር ለመቅረፍ ሲል ትርፋማ የሆኑ ድርጅቶችን ለውጭ ባለሃብቶች በሽርክና ለመስጠት መወሰኑ ከጥቅሙ ሊበልጥ እንደሚችል በማሳሰብ ላይ ናቸው።