በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 እና 10 የመልሶ ማልማት ‹‹መሰረት ድንጋይ ›› ሳይቀመጥ ቀረ

ሚያዝያ ፲፪ (አሥራ ሁለት) ቀን ፪፲፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 9 የሚገኝ 10 ሺህ ካሬ/አንድ ሄክታር/ ለሆቴል ግንባታ በካሬ 650 ሺህ ብር ሊዝ የገዙት የኳታሩ ባለሃብት ፣ አገዛዙ ቦታው ላይ የሰፈሩትን ነዋሪዎች በሙሉ አንስቶ ቦታውን አጽድቶ መጨረሱን በመግለጽ የመሰረት ድንጋይ እንዲያስቀምጡ ቢጋብዝም፣ ባለሃብቱ ግን ‹‹ህዝብ ተፈናቅሎ እያለቀሰ ባለበት ሰአት የመሰረት ድንጋይ አላስቀምጥም›› ማለታቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል።
የገዢው ፓርቲ ባለስልጣናት ባለሃብቱን ለማግባባት ተደጋጋሚ ሙከራ ያደረጉ ሲሆን፣ የኳታሩ መሪን የኢትዮጵያ ጉብኝት አስታኮ የመሰረት ድንጋይ ለማስቀመጥ ቀይ አሸዋ አፍስሰው የተጠረበ ድንጋይና ስሚንቶ አዘጋጅተው ቢጠብቁም፣ ባለሀብቱ ባለመቀበላቸው ድንጋይ የማስቀመጥ ስነስርዓቱ አልተከናወነም። የአካባቢው ነዋሪዎች መረጃውን ከክፍለ-ከተማውና የወረዳው መስተዳድር አካላት ማግኘታቸውን ተናግረዋል።
የኳታሩ ባለሃብት ያነሱትን ጥያቄ ተከትሎ የአዲስ አበባ መስተዳድር “ከዚህ በፊት የቤት ግምቱ ይሻሻላል፣ የመኖሪያ ቤት መስሪያ ምትክ ቦታ በስምምነታችሁ መሰረት ይሰጣችኋል ፣ ይህ እስኪፈጸም በግዳጅ መፈናቀል አይኖርም” በማለት ለህዝቡ በአደባባይ የገባውን ቃል አጥፎ፣ ህዝብን በመከፋፈል፣ የተሳሳተ መረጃ በመስጠትና አፍራሽ ወጣቶችን አሰማርቶ በግዳጅ ለማፍረስ ከጀመረው ድርጊት አለመቆጠቡን ነዋሪዎች ይገልጻሉ።
መስተዳድሩ ለተፈናቃዮች የተሰጠው ቤት ይህ ነው በማለት ለባለሃብቱ የልደታ ኮንዶሚንየምን ማሳየቱን የሚገልጹት ነዋሪዎች፣ “ከእኛ መንግስት ይልቅ የኳታሩ ባለሃብት ያሳዩት ‹ሰብዓዊነት› በልጦ መገኘቱ፣ ይህ መንግስት እንደ ዜጋው እየተመለከተን ነው ብለን ለመቀበል አስቸግሮናል ›› በማለት ያሉበትን አሰቃቂ ሁኔታ ገልጸዋል።
ተከራይ የቀበሌ ቤት ነዋሪዎች ሙሉ በሙሉ፣ ባለይዞታዎች ደግሞ በአብዛኛው ቤታቸውን በላያቸው ላይ አፍርሰው የግንባታ እቃዎችን በነጻ እንዲወስዱ በተፈቀደላቸው ‹አፍራሽ ወጣቶች› ፈርሶ ከአካባቢው እንዲለቁ የተደረጉ ሲሆን፣ በተለያየ ምክንያት ያለቀቁ ባለይዞታዎች የትንሣኤ በዓልን ‹‹ሌባ ሲጠብቁ ›› ማሰለፋቸውን በምሬት ገልጸዋል፡፡
እነዚሁ ባለይዞታ ነዋሪዎች — ያሉበትን አደገኛ ሁኔታ ቀኑን በሙሉ እዚያው ለሚውሉ የፖሊስ አባላት ቢያስረዱም ‹‹ እኛ ከዋናው መንገድ ወደ ውስጥ ለመግባት አንችልም፣ እኛም ለራሳችን እንፈራለን፣ አልታዘዝንም ›› በማለት መልስ መስጠታቸውን፣ ‹‹አፍራሽ ወጣቶችም ፖሊሶችን አፍርሰው ከሚያገኙት የጥቅም ተጋሪዎች እንዳደረጓቸውና ምንም እንደማይደረጉ በድፍረት የሚናገሩ መሆኑን፣ በሌላ በኩል አንዳንድ ፖሊሶች ‹‹ ይህ ወጣት የተወለደበትንና ያደገበትን ሠፈር ከማፍረስ መከላከል ሲገባው፣ ይህን ዓይነት ድርጊት ሲፈጽም እያያችሁ እኛን ምን አድርጉ ትላላችሁ›› ሲሉ በወጣቶቹ ሁኔታ ማዘናቸውን እንደገለጹላቸው አስረድተዋል፡፡