በሰሜን ጎንደር በነጻነት ሃይሎች እና በአገዛዙ ወታደሮች መካከል የሚካሄደው ጦርነት ቀጥሎ ዋለ

ኅዳር ፳ (ሃያ)ቀን ፳፻ / ኢሳት ዜና :- የአካባቢው ምንጮች እንደገለጹት በነጻነት ሃይሎች እና በገዢው ፓርቲ ወታደሮች መካከል ለሳምንታት የዘለቀው ጦርነት ዛሬ በደቡብ ጎንደርና በበለሳ መሃከል ዳዊጭ በሚባል አካባቢ ቀጥሎ ውሎአል። በሁለቱም ወገኖች ስለደረሰው ጉዳት ዝርዝር መረጃ አልደረሰንም። ይሁን እንጅ ጦርነቱ ከፍተኛ መሆኑን ምንጮች ጠቁመዋል።

በሌላ በኩል አገዛዙ ሰራዊቱን ወደ ተለያዩ አካባቢዎች እያንቀሳቀሰ ሲሆን ፣ ትናንት ሰኞ ወታደሮችን የጫኑ ኦራል መኪናዎች ቁንዝላ ከተማ መግባታቸውንና ቀድሞ የኢትዮጵያ ጦር ይጠቀምበት በነበረው የመንገድ ባለስልጣን ካምፕ ውስጥ ሰፍረዋል። ዛሬ አካባቢውን ሲያስሱ መዋላቸው ታውቋል። አካባቢው የጎንደርና የጎጃም ግዛቶች መለያ ሲሆን፣ ቀደም ብሎ የኢህአፓ ሰራዊት ይንቀሳቀስበት ነበር። የተወሰነ ሰራዊት ደግሞ ወደ ሱዳን በመግባት የነጻነት ሃይሎች ከጀርባ ለመምታት መታቀዱን ምንጮች ገልጸዋል።

በሌላ በኩል ህዳር 16 ቀን 2009 ዓም ከአገዛዙ ወታደሮች ጋር ከፍተኛ ጦርነት ያካሄደው የነጻነት ሃይል መሪ የሆኑት የታጋይ ጎቤ መልኬ ከፍተኛ ንብረት ተዘርፎ ተወስዷል። ታጋይ ጎቤ ለኢሳት እንደገለጹት የገዢው ፓርቲ ካድሬዎች ፣ 3 መኪናዎች፣ ከ400 በላይ የቀንድ ከብት፣ ከ300 በላይ ፍየሎች እንዲሁም በርካታ የጋማ ከብት ወስደዋል። 7 ሄክታር በሚደርስ መሬት ላይ የመስኖ ስራ የሚሰሩ ሰራተኞችም ተወስደው መታሰራቸውን ተናግረዋል።

በተመሳሳይ ዜና ወታደሮች  ለረጅም ጊዜ በአካባቢው የሚንቀሳቀሰውን ታጋይ ቴውድሮስ ዘመዶች አስረው አዝመራቸውን አሰብሰበው በመውቃት መውሰዳቸውን ከስፍራው የደረሰን ዜና ያመለክታል። ታጋይ ቴውድሮስን ለመያዝ የተለያዩ ሙከራዎችን ያደረጉት ወታደሮች ፣ ተስፋ በመቁረጥ የወሰዱት እርምጃ መሆኑን ምንጮች ይናገራሉ።