በሚድሮክ ወርቅ እና በሻኪሶ ህዝብ መካከል ያለው አለመግባባት ድርጅቱን አደጋ ላጥ ጥሎታል ተባለ

ግንቦት ፳፪ (ሃያ ሁለት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ንብረትነቱ የሼህ መሐመድ ሁሴን አልአሙዲ የሆነውና በሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ሥር የሚገኘው ሚድሮክ

ወርቅ ኩባንያ በሻኪሶ አካባቢ ሕገወጥ ሠፈራ ይቁምልኝ ሲል ሲያካሂድ የነበረው ሙግት በፊዴራልና የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት በኩል ተገቢውን ትኩረት ባለማግኘቱ ቢዝነሱ ሥጋት ላይ መውደቁን ምንጮች ጠቆመዋል፡፡

ሚድሮክ ወርቅ በሻኪሶ ለገደንቢ አካባቢ ሰዎች ተደራጅተው አነስተኛ ከተማ በመመሥረት ግልጽ ዘረፋ እየፈጸሙብኝ ነው ሲል ካለፉት ሶስት ዓመታት ወዲህ ለሚመለከታቸው አካላት ሁሉ አቤቱታ ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡ ኩባንያው እንደሚለው የተደራጁ ዘራፊዎች ሕጋዊ በሆነ ይዞታው ውስጥ በመግባት በቁፋሮ የወጡ ድንጋዮችን ወስደው በመከስከስ ወርቅ አምራች ነን የሚሉ ናቸው ብሏል፡፡ድርጊቱ በመስፋፋቱም አካባቢው በድንጋይ ክምር በመሞላቱ “ሮክ ሲቲ” የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል።

የሼሁ ኩባንያ ድርጊቱን እንዲያሰቆሙለት በተደጋጋሚ ለሚመለከታቸው አካላት አቤቱታ አቅርቦ አጥጋቢ ምላሸ እንዳልተሰጠው በዚህም ምክንያት ቢዝነሱ ጭምር አደጋ ላይ መውደቁን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡  ኩባንያው በአካባቢው ያለውን የወርቅ ማእድን እየዘረፈ ፣ ነገር ግን ለሻኪሶ ህዝብ ምንም ያስገኘለት ጥቅም የለም በሚል ምክንያት ከሁለት አመት በፊት የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ ዝርፊያው መባባሱ እየተነገረ ነው።

የአካባቢው ህዝብ ሚድርኦክ ኩባንያን በመቃመው ሰላማዊ ሳልፍ ባደረገበት ጊዜ የፌደራል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ የተወሰኑ ሰዎች መገደላቸውና በርካቶች ታስረው አሁንም ድረስ ፍርድ ቤት በመመላለስ ላይ ይገኛሉ። የአካባቢው ነዋሪዎች በአገኙት አጋጣሚ ሁሉ የኩባንያውን ወርቅ እየወሰዱ ተቃውሞአቸውን በመግለጽ ላይ መሆናቸውን አንድ የአካባቢው የተቃዋሚ አባል ለኢሳት መናገራቸው ይታወሳል።

ሚድሮክ ባለፈው ዓመት መጨረሻ 19 ቢሊየን ብር የሸያጭ ተስፋ ያለውና 33ሺ ኪሎግራም  የወርቅ ክምችት በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ማግኘቱን ይፋ ማድረጉ ይታወሳል፡፡

የሼሁ የወርቅ ኩባንያ በኢትዮጵያ ብቸኛ የሆነ የወርቅ ማምረት ፈቃድ ባለቤትና አምራች ሲሆን በአሁኑ ወቅት ሁለት ከፍተኛ ደረጃ ወርቅ ማዕድናት የማምረት ፈቃድ አለው፡፡በለገደንቢ የካባ ወርቅ ማዕድንና በሳካሮ የመሬት ውስጥ ለውስጥ ማዕድን ማምረቻ ነው ኩባንያው ከፍተኛ የሆነ ትርፍ እያጋበሰ ነው። ሚድሮክ ኩባንያ ስራ ከጀመረበት እኤአ 1997  አንስቶ ላለፉት 15 አመታት ከወርቅ ማእድናቱ ስላገኘው ትርፍ መረጃ ሰጥቶ አያውቅም።

ኩባንያው ስራ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ትርፋማ ቢሆንም፣ ለረጅም ጊዜ የትርፍ ግብር ከፍሎ እንደማያውቅ መረጃዎች ያመለክታሉ። ሺክ አላሙዲን በአለማችን ያለውን የሀብት መሰላል በፍጥነት እንዲወጡ ከረዷቸው ድርጅቶቻቸው መካከል ሚድሮክ ወርቅ በቀዳሚነት ይጠቀሳል።

በቅርቡ ተጨማሪ መሬቶችን ለኩባንያው ለማስረከብ በጉጂ ዞን ውስጥ በተለያዩ ቀበሌዎች የሚኖሩ አርሶአደሮች አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ ቢታዘዙም የተወሰኑ ቀበሌዎች ነዋሪዎች አሻፈረኝ ማለታቸው ይታወሳል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide