በላስቬጋስ የጅምላ ግድያን ከፈጸመው ግለሰብ የሆቴል ክፍልና ከቤቱ በአጠቃላይ 42 መሳሪያዎች ተገኙ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 23/2010)በኔቫዳ ግዛት ላስቬጋስ ከተማ የተፈጸመውና በአሜሪካ ታሪክ ከፍተኛ የተባለው የጅምላ ግድያን ከፈጸመው ግለሰብ የሆቴል ክፍልና ከቤቱ በአጠቃላይ 42 መሳሪያዎችን ማግኘቱን የግዛቲቱ ፖሊስ አስታወቀ።

በአደጋው የሞቱት ሰዎች ቁጥር 59 ሲደርስ የቆሰሉት ደግሞ 527 ደርሰዋል።

አለም አቀፉ አሸባሪ ቡድን አይ ሲስ ስቴፈን ፓዶክ እምነቱን የቀየረ አባላችን ነው ሲል መግለጫ ሰጥቷል።

የአሜሪካ ባለስልጣናት ድርጊቱን ከሽብር ጋር የሚያገናኘው ምልክት አላየንም ሲሉ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ደግሞ የድርጊቱን ፈጻሚ በሽተኛ በማለት ጠርተውታል።

ጡረተኛውና ሐብታሙ አካውንታንት የ64 አመቱ ስቴፈን ፓዶክ በበረሃማዋ ውብ የቁማር ከተማ ላስቬጋስ ውስጥ የፈጸመው ድርጊት የአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ሆኖ ቀጥሏል።

በላስቬጋስ ከተማ ማንዳላይ ቤይ ከሚባለው ሆቴል 32ኛ ፎቅ ከመኝታ ክፍሉ ውስጥ ቁልቁል በመተኮስ ፍጅት ያነገሰው የ64 አመቱ አሜሪካዊና የላስ ቬጋስ ከተማ ነዋሪ የአባቱን የባንክ ዘራፊነት የሚያስታውሱ ሪፖርቶች እንዲወጡም ምክንያት ሆኗል።

ምን እንደተፈጠረ መረዳት ቸግሮኛል በማለት በተከሰተው ሁኔታ ግራ መጋባቱን ለመገናኛ ብዙሃን የገለጸው በፍሎሪዳ ኦርላንዶ ነዋሪ የሆነው የነፍሰ ገዳዩ ወንድም ኤሪክ ፓዶክ ነው።

በግድያው ማግስት ሰኞ ለመገናኛ ብዙሃን እንደተናገረው ወንድሙ ሚሊየነርና በጡረታ ላይ የሚገኝ አካውንታንት ቢሆንም ጤናማ የሚባል አይነት ሰው አልነበረም ሲል ገልጾታል።
ቪዲዮ ፖከር በተባለው የቁማር አይነት የተለከፈ ሰው እንደነበርም ተናግሯል።

በሪል ስቴት ቢዝነስ ላይ የሚገኘው ሚሊየነሩ ስቴፈን ፓዶክ ኪሳራ ይድረስበት አይድረስበት የማውቀው ነገር የለም ያለው ኤሪክ ፓዶክ በቅርቡ ለ90 አመቷ እናታቸው ለእግር ጉዞ የሚያግዛቸው መሳሪያ በፖስታ ቤት እንደላከላቸውም ገልጿል።
በልጅነቱ ሳንቲሞችን የማጠራቀም ፍቅር እንጂ የመሳሪያ ፍላጎት እንዳልነበረውና በየትኛውም ሰራዊት ውስጥ እንዳላገለገለ ወንድሙ ኤሪክ ፓዶክ ለመገናኛ ብዙሃን ገልጿል።

59 ንጹሃን ዜጎችን በመጨፍጨፍ 527 ሰዎችን ያቆሰለው ፓዶክ ከቀደመ የቤተሰቡ ታሪኩ መረዳት እንደተቻለውም አባቱ የታወቀ የባንክ ዘራፊና በኤፍ ቢ አይ ተፈላጊዎች ዝርዝር ውስጥ የተመዘገበ ወንጀለኛ ነበር።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ1969 እስከ 1977 በአሜሪካ የፌደራል ምርመራ ቢሮ እጅግ በጣም ተፈላጊ ተብለው ከሚታደኑ 10 ወንጀለኞች የላስቬጋሱ ጨፍጫፊ ስቴፈን ፓዶክ አባት ቤንጃሚን ፓዶክ አንዱ ነበር።

ማንዳሊን ቤይ ከሚባለው ሆቴል 32ኛ ፎቅ አልጋ ከያዘበት ክፍል ቁልቁል የሙዚቃ ትርኢት ይከታተል በነበረው ሕዝብ ላይ መሳሪያ እየለዋወጠ ፍጅት ያነገሰው ስቴፈን ፓዶክ ድርጊቱን ለምን እንደፈጸመ እስካሁን የተረጋገጠ ነገር የለም።

ፖሊሶች ግለሰቡን በቁጥጥር ስር ለማድረግ በተንቀሳቀሱበት ወቅት አስቀድሞ ራሱን በመግደሉ ምርመራውን ይበልጥ ውስብስብ አድርጎታል።

አለም አቀፉ የሽብር ቡድን አይ ሲስ ስቴፈን ፓዶክ እምነቱን ወደ እስልምና የቀየረ አባላችን ነው በማለት ለድርጊቱ ሃላፊነቱን ወስዷል።

ጥምሩ ሃይል ለከፈተብን ጥቃት አጸፋ ነው ሲልም በድርጊቱ መደሰቱን ገልጿል።

የአሜሪካ ባለስልጣናት ጉዳዩ እየተመረመረ መሆኑን የገለጹ ሲሆን ሆኖም ድርጊቱ ከየትኛውም የሽብር ቡድን ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚያመላክት ምንም አይነት ፍንጭ አለማግኘታቸውን አስታውቀዋል።