ሼባ ሌዘር ኢንደስትሪ አዲስ ፋብሪካ አስመረቀ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 23/2010)የኤፈርት ኩባንያ አካል የሆነው ሼባ ሌዘር ኢንደስትሪ አዲስ ፋብሪካ አስመረቀ።

አዲሱ ፋብሪካ ለውጭ ገበያ በሚያቀርበው ምርት በአመት ከ36 ሚሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምናዛሪ ያገኛል።

በኤፈርት ዋና ስራ አስፈጻሚ ወይዘሮ አዜብ መስፍንና በኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር መብራሕቱ መለስ መስከረም 22 በትግራይ ውቅሮ ከተማ የተመረቀው ይህ ፋብሪካ ለውጭ ገበያ ከሚያቀርባቸው ቆዳ ጫማዎች በተጨማሪ ያለቀላቸው የሴቶች የእጅ ቦርሳዎችን ያመርታል።

የህወሃት ፖሊት ቢሮ አባልና የኤፈርት ዋና ስራ አስፈጻሚ የሆኑት ወይዘሮ አዜብ መስፍን በማምረቻ ፋብሪካው ምርቃት ላይ ይሄ ፋብሪካ በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ በጥራት ደረጃው ተወዳዳሪ የሌለው ነው ሲሉ ተደምጠዋል።
በመርፌ አይን የማለፍ ያህል ከባድ የሆነውን የአለም ገበያ ሰብሮ መግባቱ ከፍተኛ ደስታን ፈጥሮልኛልም ብለዋል።

የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር መብርሃቱ መለስ በሀገር ደረጃ ከዚህ ሴክተር የምናገኘው የውጭ ምንዛሪ ከ2 ሚሊየን ዶላር በታች መሆኑን ገልጸዋል።

ይህ አዲሱ የኤፈርት አካል የሆነው ፋብሪካ በወር እስከ 3 ሚሊየን ዶላር የሚያስገኝ በመሆኑ የውጭ ምንዛሪ ገቢያችንን ከ100 ፐርሰንት እጥፍ በላይ ያሳድገዋል ብለዋል።
ፋብሪካው በአንድ የጂቲፒ ጊዜ እስከ 1 ቢሊየን ዶላር የውጭ ምንዛሪ እንደሚያስገኝ ተናግረዋል።

ፋብሪካው በአመት እስከ 100 ሺ ቦርሳዎችን በማምረት በአሜሪካ ኒዮርክ ከተማ ለገበያ እንደሚያቀርብ የተናገሩት የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ዮሀንስ ካሳሁን ለዚህ ደግሞ የኤም ላንደር የተባለ የአሜሪካን ኩባንያ ገበያውን ሊያመቻች ሽርክና መፍጠራቸውን ተናግረዋል።

በአምስት አመት ውስጥ ምርቱን እየጨመረ እስከ 1 ሚሊየን ቦርሳዎችን ወደ ውጭ በመላክ 25 ሚልየን የአሜሪካን ዶላር ያህል ገቢ እንደሚያስገኝም ገልጸዋል።

ወይዘሮ አዜብ መስፍን ባለቤታቸው የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ ከመሞታቸው በፊት ትግራይን የኢንደስትሪና ፋብሪካ ማዕከል ለማድረግ የሚያስችል እቅድ መንደፋቸውንና የእሳቸውም ተልእኮ ይህንን እቅድ ወደ ተግባር መቀየር እንደሆነ መግለጻቸው የሚታወስ ነው።