ለኢትዮጵያ የአባይ ጉዳይ የሞትና የሽረት ጉዳይ ነው ተባለ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 14/2010) የአባይ ጉዳይ ለእኛም የሞትና የሽረት ጉዳይ ነው ሲሉ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ገለጹ።

ቃል አቀባዩ አቶ መለስ አለም የአባይ ግድብን በተመለከተ ከግብጽ ጋር ውጥረት መከሰቱን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት ኢትዮጵያ በራሷ አቅም አባይን መገደቧን ትቀጥላለች።

የግብጹ ፕሬዝዳንት አልሲሲ በቅርቡ አንድ የአሳ ፋብሪካን ሲመርቁ አባይ የህይወትና የሞት ጉዳይ ነው ማለታቸው ይታወሳል።

ኢትዮጵያ እየገነባች ባለችው የአባይ ግድብ የተነሳ ግብጽ ሰሞኑን ጠንካራና ጠጠር ያለ ቃላት በመወርወር ላይ ትገኛለች።

ይህ ደግሞ በኢትዮጵያ ፣ግብጽና ሱዳን መካከል የተጀመረው ውይይት እንከን ስለገጠመው መሆኑ ነው የተነገረው።

ግብጽ በሶስትዮሹ ምክክር ከዚህ ቀደሞ የነበሩ የቅኝ ግዛት ውሎች ግምት ውስጥ ይግቡልኝ ስትል ኢትዮጵያና ሱዳን ሀሳቡን አልተቀበሉትም ነበር።

እናም በዚሁ ሳቢያ እሰጣ ገባ የገቡት የሶስቱ ሀገራት የውሃ ሚኒስትሮች በካይሮ ያካሄዱት ውይይት መቋረጡ ለሰጣ ገባው ምክንያት ሆኗል።

የግብጹ ፕሬዝዳንት አልሲሲ ታዲያ የውይይቱን መቋረጥ ተከትሎ ማስጠንቀቂያ አዘል ሀሳብ ሰንዝረዋል።

አልሲሲ በቅርቡ አንድ የአሳ ፋብሪካ በሀገራቸው ሲመርቁ እንዳሉት የአባይ ጉዳይ ለግብጽ የሞትና የሽረት ጉዳይ ነው።

ይህ ጠንከርና ጠጠር ያለው የአልሲሲ ንግግር ታዲያ ኢትዮጵያን ተመሳሳይ ቃላት እንድትሰነዝር አስገድዷታል።

የኢትዮጵያው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አቶ መለስ አለም ጉዳዩን አስመልክቶ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የአባይ ጉዳይ ለኢትዮጵያም የሞትና የሽረት ጉዳይ ነው።

እናም ግብጽ የሶስቱን ሀገራት የቀድሞ ስምምነት በሚጥስ መልኩ መግለጫ መስጠቷ የተሳሳተ ነው ብለዋል።

በግብጽ በኩል እየተሰነዘረ ያለው የማስጠንቀቂያ ቃላት ኢትዮጵያ የአባይን ግድብ እውን የምታደርግ ከሆነ የውሃው መጠን ቀንሶ ህልውናችንን ስጋት ውስጥ ይከታል በሚል ነው።

የሕዳሴው ግድብ ተብሎ የሚታወቀውን ግንባታ ከ60 በመቶ በላይ ማጠናቀቋን የምትገልጸው ኢትዮጵያ ግን ስራው እንደሚቀጥል አስታውቃለች።

ሱዳን በበኩሏ ኢትዮጵያ ግድቡን መገደቧ በተፋሰሱ ሀገራት ላይ የሚያስከትለው ችግር አይኖርም ባይ ነች።

በዚህ የሱዳን አቋም ሳቢያም ግብጽ የካርቱም መንግስት ለኢትዮጵያ እያደላ ነው በሚል ቅሬታዋን ገልጻለች።

ግብጽ የአባይ ግድብን ለማስቆም ወታደራዊ አማራጭ የምትከተል ከሆነ አካባቢው ወደ ከፋ ጦርነት ሊሸጋገር ይችላል በሚል ዘገባዎች ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።