የአውሮፓ ፓርላማ ከህዝባዊ ተቃውሞ ጋር በተገናኘ የተፈጸመው ግድያ በገለልተኛ አካል እንዲጣራ ያቀረበው ጥያቄ ተግባራዊ እንዲደረግ ተጠየቀ

ኢሳት (ግንቦት 11 ፥ 2009)

የአውሮፓ ፓርላማ በኢትዮጵያ ከህዝባዊ ተቃውሞ ጋር በተገናኘ የተፈጸመው ግድያ በገለልተኛ አካል እንዲጣራ ሃሙስ ያቀረበው ጥያቄ ተግባራዊ መደረግ እንዳለበት ሂውማን ራይትስ ዎች አሳሰበ።

ፓርላማው ያቀረበው ይኸው ወቅታዊ ጥሪ ጉዳዩ የአውሮፓ ህብረት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት በቀጣዩ ወር በጀኔቭ ከተማ በሚካሄደው ጉባዔ ላይ ተጨማሪ እርምጃ እንዲወስድ ሊያደርግ የሚያስችል መሆኑን በድርጅቱ የአፍሪካ ቀንድ ተመራማሪ የሆኑት ፊሊክስ ሆንር አስታውቀዋል።

ከአውሮፓ ፓርላማ በትናንትናው ዕለት ያቀረበው ጥሪ በኢትዮጵያ ከተጠያቂነት ለማምለጥ ለሚደረገው ጥረት ትኩረትን የሚሰጥ እንደሆነም ሃላፊው አክለው አስረድተዋል።

ሂውማን ራይትስ ዎች እና ሌሎች የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ከአመት በፊት በኢትዮጵያ የተፈጸመው ግድያና የጅምላ እስራት በአስቸኳይ በገለልተኛ አካል ማጣራት እንዲካሄድበት ሲጠይቁ መቆየታቸው ይታወሳል።

ይሁንና የመንግስት ባለስልጣናት ጥሪውን ሳይቀበሉ የቀረ ሲሆን፣ መንግስታዊው የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ተካሄዷል ባለው ምርመራ 745 ሰዎች መገደላቸውን በቅርቡ አስታውቀዋል።

የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ምርመራን ለማካሄድ ያቀረበው ጥያቄ ተቀባይነት ባለማግኘቱ በኮሚሽኑ የቀረበውን ሪፖርት እውቅና እንደማይሰጠው ይፋ ማድረጉም አይዘነጋም።

አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ከህዝባዊ ተቃውሞ ጋር በተገናኘ በመንግስት የተገለጸው የ745 ሰዎች መሞት አነስተኛ ሊሆን እንደሚችል በመግለጽ ላይ ናቸው።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ገለልተኛ ምርመራን ለማካሄድ ጥሪውን በድጋሚ ያቀረበ ሲሆን፣ የአውሮፓ ፓርላማም ድርጊቱን በገለልተኛ ቡድን ምርመራ መካሄድ እንዳለበት ሃሙስ ባወጣው መግለጫ አሳስቧል።

ከተለያዩ አለም አቀፍ አካላት እየቀረበ ስላለው ለዚሁ ጥሪ መንግስት እስካሁን ድረስ የሰጠው ምላሽ የለም።