የአውሮፓ ህብረት ዶ/ር መረራ ጉዲናን አስመልክቶ ያወጣው መግለጫ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለማሳነስ የሞከረ ነው ሲል የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቅሬታ አቀረበ

ኢሳት (ግንቦት 11 ፥ 2009)

የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአውሮፓ ፓርላማ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታዩ ባሉት ዶ/ር መረራ ጉዲናን አስመልክቶ ያወጣው መግለጫ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለማሳነስ የሞከረ ነው ሲል አርብ ቅሬታ አቀረበ።

ህብረቱ የህግ አውጪ አካል የሆነው የአውሮፓ ፓርላማ የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ ካልተገነዘቡ አባላቱ እይታ ተነስቶ ያወጣው መግለጫ ነው ሲልም የውጭ ጉዳይ ሚኒቴር አመልክቷል።

የአውሮፓ ፓርማላ ሃሙስ ባወጣው መግለጫ ዶ/ር መረራ ጉዲና ላይ የተመሰረተው ክስ ውድቅ ተደርጎ በአስቸኳይ እንዲለቀቁ ጥያቄ ማቅረቡ ይታወሳል።

ፓርላማው ከወራት በፊት ዶ/ር መረራ ጉዲናን በዋናው ጽ/ቤቱ በመጋበዝ በወቅታዊ የኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ምክክር ማካሄዱ ይታወሳል።

ይሁንና የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) አመራሩ ከዚሁ ግብዣ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ በተመለሱ ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጥሰዋል ተብለው ለእስር መዳረጋቸው ይታወሳል።

የፌዴራሉ ከሳሽ አቃቤ ህግ ዶ/ር መረራ ጉዲና በአውሮፓ ቆይታቸው ከአርበኞች ግንቦት 7 አመራር ጋር ተገናኘተዋል ሲል የእስሩን መንስዔ አብራርቷል።

በኦሮሚያ ክልል ሲካሄድ የቆየውን ህዝባዊ ተቃውሞ ጭምር አባብሰዋል የሚል የቀረበባቸው ክስ በማስተባበል ባለፈው ሳምንት ለፍርድ ቤት ምላሽን አቅርበዋል።