ኦህዴድ የውስጠ ድርጅት ቀውስ ውስጥ መሆኑ ተገለጸ

(ኢሳት ዜና–ጳጉሜ 2/2009) በዘርፈ ብዙ ግጭቶችና ህዝብ ተቃውሞ እየታመሰ ያለው ኦህዴድ የውስጠ ድርጅት ቀውስ ውስጥ መሆኑ ተገለጸ።

ባለፉት ተከታታይ ወራት የስርአት ለውጥ በሚጠይቁ ዜጎች ህዝባዊ ተቃውሞ የገጠመው የኦሮሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት/ኦህዴድ/ ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ከድርጅቱ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ ጀምሮ የ18 ከፍተኛ ባለስልጣናትና ካድሬዎች ለውጥ አድርጓል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በህወሃት ወታደራዊ አዛዦች በሚመራው የሱማሌ ልዩ ፖሊስና በኦሮሚያ ህዝብ መካከል እየተካሄደ ያለው ግጭት ተባብሶ መቀጠሉን የደረሱን መረጃዎች አመላክተዋል።

ኦህዴድ በሕወሃት ከተፈጠረበት እለት አንስቶ በኦሮሞ ህዝብ ተቀባይነት ባለማግኘቱ ምክንያት በተደጋጋሚ ጊዜ የአመራር ለውጥ ቢያደርግም በውስጡ ያሉት ችግሮች የበለጠ እየተባባሱ መሔዳቸውን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

በሕወሃት ውሳኔ የተካሄደው ይህ የፖሊት ቢሮ፣የድርጅትና የመንግስት ቢሮ ሃላፊዎችን የመቀየር ስራ በህዝቡ የስርአት ለውጥ ትግል ላይ የሚፈይደው ነገር እንደሌለ ምንጮቹ አመልክተዋል።

የኦሮሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት/ኦህዴድ/ ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ከድርጅቱ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ ጀምሮ የ18 ከፍተኛ ባለስልጣናትና ካድሬዎች ለውጥ አድርጓል።

በህወሃት ጉዳይ አስፈጻሚነት በኦህዴድ ካድሬዎችና አባላት የሚታወቁት አቶ አብዱላዚዝ መሀመድ፣አቶ ፍቃዱ ሰማና ወይዘሮ አዳነች አቤቤ ወደ ስራ አስፈጻሚነት እንዲመጡ ተደርጓል።ይህ ደግሞ የእነ አባይ ጸሐዬን ፍላጎት የሚያመላክት መሆኑ ተጠቁሟል።

በፊንፊኔ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ዋና አስተዳዳሪ የተደረጉት አቶ ሙስጠፋ አባሲማልና የቡራዩ ከተማ ከንቲባ ሆነው የተመደቡት አቶ ፈይሳ አሰፋ ከክልሉ ፕሬዝዳንት ለማ መገርሳና የደህንነት ጽህፈት ቤት ጋር ልዩ ግንኙነት እንዳላቸው የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

አቶ አባይ ጸሃዬ በአዳማ በተካሄደ ስብሰባ ላይ በኦሮሚያ ዋነኛ ችግር ፈጣሪዎቹ በፊንፊኔ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን አመራሮች መሆናቸውን በመግለጽ ልክ እንደሚያስገቧቸው መዛታቸው ይታወሳል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በህወሃት ወታደራዊ አዛዦች በሚመራው የሱማሌ ልዩ ፖሊስና በኦሮሚያ ህዝብ መካከል እየተካሄደ ያለው ግጭት ተባብሶ መቀጠሉን የደረሱን መረጃዎች አመላክተዋል።

ትላንት ምሽት በኦሮሚያ ክልል በቦረና ዞን በተፈጠረ ግጭት ከሁለቱም ወገኖች ከ20 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተግልጿል።

ኢሳት ጉዳቱ እስከምንድረስ ነው የሚለውንና ትክክለኛውን የሟቾች ቁጥር ለማጣራት ያደረገው ሙከራ አልተሳካም።