በፍሎሪዳ ኢርማ አውሎ ንፋስ 25 በመቶ የሚሆኑ መኖሪያ ቤቶችን ከጥቅም ውጪ ማድረጉ ተሰማ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 2/2010) በአሜሪካ የፍሎሪዳ ግዛትን የመታው ኢርማ አውሎ ንፋስ 25 በመቶ የሚሆኑ መኖሪያ ቤቶችን ከጥቅም ውጪ ማድረጉ ተሰማ።

የሀገሪቱ የፌደራል የአስቸኳይ ጊዜ መስሪያ ቤት 65 በመቶ የሚሆኑት መኖሪያ ቤቶችም ከባድ በሚባል ሁኔታ መጎዳታቸውን አስታውቋል።

60 በመቶ የሚሆኑ ነዋሪዎች እስካሁን ከኤሌክትሪክ አገልግሎት ውጪ ሆነው በጨለማ እንደተዋጡ ናቸው ይላል ቢቢሲ በዘገባው።

በፍሎሪዳ ከአውሎ ንፋሱ ጋር በተያያዘ 6 ሰዎች ሕይወታቸውን ማጣታቸውም ታውቋል።

አሁን ላይ ፍጥነቱን በሰአት ወደ 95 ማይልስ በመቀነስ ጉዞውን ወደ ደቡብ ደቡብ ምእራብ አትላንታ ጆርጂያ ያደረገው ኢርማ አውሎ ንፋስ ወደ አልባማ ብሎም ወደ ምዕራብ ቴንሴ ሊያቀና እንደሚችል ሲ ኤን ኤን በዘገባው አስፍሯል።