በዶክተር መረራ ጉዲና ላይ የአቃቢ ህግ ምስክሮች ተሰሙ

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 24/2010)በኦፌኮ ሊቀመንበር ዶክተር መረራ ጉዲና ላይ የአቃቢ ህግ ምስክሮች ተሰሙ።

ዶክተር መረራ እጃቸውን በብረት ካቴና እንዳይታሰሩ ለፍርድ ቤት ያቀረቡት የአቤቱታ ደብዳቤ ይፋዊ ምላሽ አላገኘም።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅን በመተላለፍ የወንጀል ክስ የቀረበባቸው የኦሮሞ ፌደራሊስ ኮንግረስ ሊቀመንበር ዶክተር መረራ ጉዲና የእምነት ክህደት ቃላቸውን ጥቅምት 6/2010 በሰጡበት ወቅት ድርጊቱን አልፈጸምኩም፣ጥፋተኛም አይደለሁም ማለታቸውን ተከትሎ አቃቢ ህግ ምስክሮችን ለጥቅምት 24/2010 አቅርቦ እንዲያሰማ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር።

ይህን ትዕዛዝ ተከትሎ የፌደራሉ አቃቢ ህግ ሁለት የደረጃ ምስክሮችን አሰምቷል።

መጠሪያቸው ደራራና ጌታቸው እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ የገለጹት ምስክሮች ታህሳት 14/2009 ዶክተር መረራ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ከኮምፒዩተር የወጣውን ጽሁፍ የራሴ ነው ብለው ሲፈርሙ ተገኝተን ታዝበናል ብለዋል።

አንደኛው ምስክር የዶክተር መረራ ነው ከተባለ ኮምፒዩተር ፕሪንት ተደርገው የወጡ ጽሁፎችን በከፊል እንዳነበበ መስክሯል።

በተቃራኒው ሁለተኛው ምስክር የጽሁፎቹን ይዘት ብቻ ሳይሆን ርዕሶቹንም አላማንበባቸውን ለፍርድ ቤቱ ገልጸዋል።

በዶክተር መረራ ላይ ይቀርባሉ ተብለው የነበሩት ተጨማሪ ምስክሮችን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳላገኛቸው ለፍርድ ቤቱ አስታውቋል።

ፍርድ ቤቱ ቀሪ ምስክሮችን ለመስማት ለህዳር 21/2010 ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ዶክተር መረራ ጉዲና ጥቅምት 7/2010 ለፍርድ ቤቱ በጻፉት የአቤቱታ ደብዳቤ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ እጃቸው በብረት ካቴና እንዳይታሰርና በማረሚያ ቤት ጎብኝዎቻቸው ብዛት ላይ ገደብ እንዳይደረግ ያቀረቡት ጥያቄ እስካሁን ምላሽ እንዳላገኘ ለማወቅ ተችሏል።

ዶክተር መረራ በአቤቱታ ደብዳቤያቸው የስኳር ህመም ታካሚ በመሆናቸው በብረት ካቴና ሲታሰሩ የሚፈጥረው ቁስለት በጤንነታቸው ላይ አደጋ እያስከተለ መሆኑን ገልጸዋል።

እጃቸው በብረት ካቴና መታሰሩ ምንም የህግ ድጋፍም ሆነ አሳማኝ ምክንያት እንደሌለው ተናግረዋል።

ዶክተር መረራ ጉዲና 4 ጠበቆች ያሏቸው ቢሆንም ገብተው መጠየቅ የሚችሉት ግን አንድ ጠበቃ ብቻ መሆናቸው ታውቋል።

የቅርብም ሆነ የሩቅ ዘመድ ወዳጆቻቸው ለመጠየቅ እንዳልተፈቀደላቸው ለማወቅ ተችሏል።