በአማራና በትግራይ አስተዳደሮች በሕዝብ ስም የተጠራው የግንኙነት መድረክ የሕወሃትን ስልጣን ለማራዘም ነው ተባለ

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 7/2010)በአማራና በትግራይ አስተዳደሮች በሕዝብ ስም የተጠራው የግንኙነት መድረክ የሕወሃትን ስልጣን ለማራዘም የታቀደ በመሆኑ እናወግዛለን ሲል የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት ልሳነ ግፉአን ማህበር ገለጸ።

የማህበሩ አመራሮች ለኢሳት እንደገለጹት የአማራን ሕዝብ በጠላትነት የፈረጀው ሕወሃት ሳይወገድ ከትግራይ ሕዝብ ጋር ድርድር ማድረግ ከጠላት ጋር እንደመተባበር ይቆጠራል።

እናም የአማራ ሕዝብ ወልቃይትን ጨምሮ በሕወሃት የተወሰደበት መሬት እስኪመለስና በአገዛዙ የደረሰበት በደል እስኪወገድ ድረስ ትግሉን እንዲቀጥል ልሳነ ግፉአን ጥሪ አቅርቧል።

በትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አባይ ወልዱ የተመራ የልኡካን ቡድን ነገ አርብ ይጀመራል ተብሎ በሚጠበቀው መድረክ ለመገኘት ጎንደር ይገባል።

የትግራይና የአማራ ክልሎች አስተዳደሮች ባዛጋጁት መድረክ ላይም ከ1 ሺ በላይ ተሳታፊዎች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ለዚሁም ከአማራና ትግራይ ክልሎች የተውጣጡ ካድሬዎችና የሀገር ሽማግሌዎች ባህላዊ አልባሳት እየታደላቸው ወደ ጎንደር እየተመሙ መሆናቸው ነው የተነገረው።

ይሄው ከኦሮሚያና ከአማራ የሕዝብ ለሕዝብ ቀጥሎ የተዘጋጀው መድረክ ከወዲሁ ተቃውሞ እየደረሰበት ይገኛል።

የወልቃይት ጠለምት ጠገዴ ልሳነ ግፉአን ማህበር ሕወሃት ሳይወገድ ድርድር ብሎ ነገር የለም በሚል መግለጫ አውጥቷል።

የማህበሩ አመራሮች አቶ ቻላቸው አባይና አቶ እንዳልካቸው ንጉሴ ለኢሳት እንደገለጹት ይህ የትግራይና የአማራ አስተዳደሮች ያዘጋጁት መድረክ አላማው የሕወሃትን እድሜ ማራዘም ነው።

አቶ ቻላቸው እንዳሉት ሕወሃት የአማራን ሕዝብ ጠላት አድርጎ የፈረጀና መሬቱንም በሃይል የቀማ በመሆኑ በቅድሚያ ሊወገድ ይገባል።

አቶ እንዳልካቸው ንጉሴ በበኩላቸው እንዲህ አይነቱ መድረክ ሕዝብን ከሕዝብ ጋር የሚያቀራርብ ቢሆንም በጎንደር የተዘጋጀውን ግን እንቃወማለን ብለዋል።

ለዚህም ምክንያት ያደረጉት ሕወሃት በወገናችን ላይ የዘር ማጥፋት ስለፈጸመ ነው ባይ ናቸው።

በጎንደር ከተማ ለ3 ቀናት ይካሄዳል የተባለውን የትግራይና የአማራ የግንኙነት መድረክ መላው የአማራ ሕዝብ እንዲያወግዘው ልሳነ ግፉአን ጥሪ አቅርቧል።